የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ቡድን የሁዋዌ “ቴክ ፎር ጉድ ግሎባል – Tech4Good” ውድድርን አንደኛ በመሆን አሸንፈዋል። ከቡድኑ አባላት መካከል አንዱ የሆነው አብዲ ገረመው ሲሆን፤ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር #INSA በ2016 ዓ.ም ባካሄደው የሳይበር ታለንት ሰመር ካምፕ ፕሮግራም ከተሳተፉና ከተመረቁ ባለ ልዩ ተሰጥኦ ወጣቶች መካከል አንዱ ነው፡፡ አብዲ ገረመው ከውድድሩ በኋላ ባስተላለፈው መልዕክት በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የሳይበር ልሕቀት ማዕከል ያሳለፈው ጊዜ ውድድሩን ለማሸነፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳበረከተለት ገልጿል፡፡
ውድድሩ በቻይና ቤጂንግ እና ሼንዘን የሚገኙ የቴክኖሎጂ ማዕከሎችን ጉብኝትና የተግባር ስልጠናዎችን ካካተተው ዝግጅት ጋር የተካሄደ ነው።
በስድስት ተማሪዎች የተወከለው የኢትዮጵያ ቡድን ተማሪዎቹን ያሰባሰበው፤ ከአዲስ አበባ፣ ከሐረማያ፣ ከጅማ፣ ከወልቂጤ እና ከአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ (AASTU) ዩኒቨርስቲዎች ነው።
ቡድኑ በውድድሩ ከሞሮኮ፣ ደቡብ አፍሪካ፤ አርጀንቲና፣ አየርላንድ፣ ማላዊ፣ ቬትናም፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስና ሌሎችን ጨምሮ ከዓለም ዙሪያ ከተውጣጡ 12 ልዩ ቡድኖች ጋር ተወዳድሯል።
የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ቡድን አሸናፊ የሆነው የእንስሳትን ህመሞች አስቀድሞ ለመለየት በተዘጋጀውና በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) በጎለበተው ኧርሊ ቬት (EarlyVet) በተሰኘው ፕሮጀክታቸው ነው፡፡
ይህ የፈጠራ ፕሮጀክት ከተባበሩት መንግስታት የዘላቂ ልማት ግቦች (SDGs) በተለይም ግብ 2 ” ዜሮ ርሃብ ” እና ግብ 15 ” ህይወት በምድር ” ከሚለው ጋር የተጣጣመ መሆኑና በግብርና እና በእንስሳት ጤና ላይ ያሉ ወሳኝ ተግዳሮቶችን ይፈታል ተብሎ እንደሚታመን በውድድሩ ተብራርቷል።
