ካቮድ ኮሜርሺያል በአዲስ አበባ መገናኛ አካባቢ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የመኪና መሸጫና መለዋወጫ ማዕከል (ካር ሞል) ግንባታን በይፋ ጀመረ።
ካቮድ ኮሜርሺያል የሽያጭ ክፍል ኃላፊ የሆኑት ወ/ሮ ሰብለወንጌል አያሌው እንደገለጹት፣ “ካር ሞል” የመኪና ማሳያ ቦታዎችን፣ የመለዋወጫ ሱቆችን፣ የመዝናኛ ስፍራዎችን፣ የታክሲና የባስ ተርሚናልን፣ የኤሌክትሪክ ተሸከርካሪ መሙያ ጣቢያዎችን (ቻርጂንግ ስቴሽኖች) እና ዘመናዊ የመኪና ማጠቢያን ጨምሮ በርካታ አገልግሎቶችን ያጠቃልላል።
ይህ ፕሮጀክት የከተማዋን የፓርኪንግ መጨናነቅ ለመቀነስና ለብዙ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ትልቅ አስተዋጽኦ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል።
በ16,300 ካሬ ሜትር ላይ የሚያርፈው ይህ ሞል ከ6 እስከ 9 ወራት ባለው ጊዜ ውስጥ ተገንብቶ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል።
ካቮድ ኮሜርሺያል ከዚህ በተጨማሪ ሽሮ ሜዳ ላይ ጥበብ ሞልን፣ ካዛንቺስ ላይ ካቮድ ሞልን፣ በአፍንጮ በር ደግሞ ስጦታ ሞልን ጨምሮ ሌሎች ዘመናዊ የንግድ ማዕከላትን እየገነባ ይገኛል።
