የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በአካል መሄድ ሳይጠበቅባቸው የነዋሪነት መታወቂያቸውን ከፋይዳ ብሔራዊ መታወቂያ ጋር የሚያስተሳስሩበት የ‘ኦንላይን’ አሠራር እየተዘረጋ እንደሆነ የአዲስ አበባ የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ አስታውቋል፡፡
የኤጀንሲው ምክትል ዋና ዳይሬክተር እና የወሳኝ ኩነት እና የነዋሪነት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ጥጋቡ ሹመይ፤ አዲሱ የ ‘ኦንላይን’ የአሰራር ስርአት በቅርቡ ባንኮች አካውንትን ከፋይዳ ጋር ለማስተሳሰር ከጀመሩት አሠራር ጋር ተመሳሳይ ይዘት ያለው ሲሆን፥ ደንበኞች በያሉበት ሆነው አገልግሎቱን እንዲያገኙ ያስችላቸዋል ተብሏል።
አሁን ላይ በ90 የከተማዋ ወረዳዎች ከፋይዳ ጋር የተሳሰረ ደኅንነቱ የተጠበቀ አዲስ መታወቂያ የመስጠት ሥራ በስኬት እየተከናወነ ቢሆንም፥ እስካሁን መታወቂያ ማስተሳሰር የሚቻለው በአካል ብቻ እንደሆነ ኃላፊው ጠቁመዋል።
ይህ ዲጂታል አሠራር በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጠናቆ ወደ ሥራ ሲገባ ኤጀንሲው የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች በቀላሉ ተደራሽ እንደሚያደርግ ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አስረድተዋል።
አቶ ጥጋቡ አክለውም፥ በቅርብ ወራት ውስጥ ማንኛውም የአዲስ አበባ ነዋሪ ወደ ወረዳ መዋቅሮች ሳይንከራተት የሚፈልገውን አገልግሎት በሙሉ ባለበት ሆኖ መጨረስ የሚችልበት እድል መፈጠሩን አረጋግጠዋል።
