የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ፤ የሰነዶች ምዝገባ እና ማረጋገጥ አገልግሎት እንዲሁም የፍትህ ሚኒስቴር ይህን የዲጅታል የሰነዶች ማረጋገጥ እና የዲጅታል ፊርማ አገልግሎት ወደ ስራ አስገብተዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርሃኑ ጸጋዬ ይህ አገልግሎት ከሐገር ውጭ ሰነድ እና ዶክመንቶች ለማረጋገጥ በሚፈልጉ ደንበኞች ቅሬታ የሚቀርብበት አገልግሎት ነበር ብለዋል።
ሚኒስትር ዴኤታው ፤የውጭ ጉዳይ አገልግሎት የውክልና እና የሰነድ ማረጋገጥ ዲጅታላይዝድ መሆኑ በአለም አቀፍ ደረጃ ያለውን ስራ በማቅለል ንግድ ኢኮኖሚ ፤ ማህበራዊ ጉዳይ ያሻሽላል ብለዋል።
ፍትሀዊ እና ቀላል፤ የሰነድ ማጭበርበር እና ሌላውንም አገልግሎት ፤ ምቹ በማድረግ የወረቀት ስራ ከነአካቴው የሚያስቀር ነው የተባለውን ቴሌ ሳይን አገልግሎት ኢትዮ ቴሌኮም አቅርቧል።
የ ኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ ፤ ይህ የዲጅታል የሰነድ ማረጋገጫ መንገድ አሰራርን አዘምኖ ቴክኖሎጂ የበላይ ሆኖ ብሄራዊ ደህንነት እንዲፈጠር ያደርጋል ብለዋል።
የዲጅታል መታወቂያን መሰረት በማድረግም የተለያዩ ማጭበርበሮችን ያስቀራል ተብሏል።
በተለይ በሀሰተኛ እና በፎርጅድ የተጥለቀለቀውን የሰነድ ማረጋገጥ እና ተያያዥ ስራዎችን ሁሉ ያጠራል መባሉን ሰምተናል።
ቴሌ ሳይን ፤ ከፍትህ ሚኒስቴር፤ ከሰነዶች ምዝገባና ማረጋገጫ እንዲሁም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር በመተባበር ከአለም አቀፍ ህጎች ጋር የተጣጣመና ደህንነቱም የተጠበቀ ነው መባሉንም ሰምተናል።
አገልግሎቱ በ ኢትዮ ቴሌኮም ክላውድ ላይ በመሆኑ የሀገርን ዳታ ሉአላዊነት በማስጠበቅ፤ ሌሎች ሀገሮችም ሊመለከቱት ፤ ሊበረብሩት ሊፈትሹት የማይችሉት ነው ተብሏል።
ይህ የ ኦንላይን አገልግሎት የኤሌክትሮኒክስ ፊርማዎችን በማካተት ማንኛውም ግለሰብ በአለበት በመፈረም አገልግሎቱን ማግኘት ይችላል ሲባል ሰምተናል።
ለዚህ ዲጅታል አገልግሎት እና ሰነድ ማረጋገጥ ፊርማው ሁለት አይነት ሲሆን የአምስት ሰከንድ የቪዲዮ ፊርማ እና የኤሌክትሮኒክስ ፊርማ የያዘ ነው።
ክፍያውም በቴሌ ብር የሚከናወን ነው ተብሏል።
ቴሌ ሳይን የዲጅታል አገልግሎት ግዜ ይቀንሳል፤ ወጭ ይቆጥባል፤ ግልፅነት ይኖረዋል፤ የአገልግሎት ጥራትንም ያመጣል ተብሏል።
ሸገር 102.1
