በአለም እግር ኳስ ላይ ከፍተኛ አስተዋጾ ያደረጋሉ ከሚባሉ ሀገራት መካከል አንዷ የሆነችው ዩናይትድ ኪንግደም የ2035 የሴቶች የአለም ዋንጫን ለማዘጋጀት ለፊፋ ጥያቄ እንዳቀረበች ታውቋል፡፡
የእንግሊዝ፣ የዌልስ፣ የስኮትላንድ እና የሰሜን አየርላንድ የእግር ኳስ ማህበር ውድድሩን በጋራ ለማስተናገድ ፍላጎት እንዳለቸው መግለጫ አውጥዋል፡፡
ይህም የሚሳካ ከሆነ እንግሊዝ የሴቶች የአለም ዋንጫን ስታሰናዳ ለመጀመሪያ ጊዜ ይሆናል፡፡
እ.ኤ.አ. 2035 ላይ ሊደረግ ለታሰበው የሴቶች የአለም ዋንጫ ጥያቄ ያቀረቡ ሀገራትን ለመመልከት በፊፋ ምክር ቤት አዘጋጅነት ስብሰባ እንደተቀመጡ ተነግሯል፡፡
አለም አቀፉ የእግር ኳስ አስተዳዳሪ (ፊፋ) እንዳለው ከዩኤፍ እና ከካፍ የተገኙ አባል ሀገራት ለዚህ ውድድር ተሳትፎ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
በዚህም ፊፋ በ2031 እና 2035 የሴቶች የአለም ዋንጫን የሚያዘጋጁ ሀገራትን በ2026 ይፋ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ዩናይትድ ኪንግደም ጥያቄ ማቅረቧን ተከትሎ የሀገሪቷ ጠቅላይ ሚኒስትር ኪየር ስታርመር እንዳሉት “የፊፋ የሴቶች የዓለም ዋንጫ 2035 በሀገራችን ለማዘጋጀት ጥያቄ ማቅረባችን በስፖርት ታሪካችን ውስጥ ሌላ ትልቅ እንድምታ ይኖረዋል፣ እድገትን የሚያመጣ እና ዘላቂ ትሩፋት የሚይዝ ነው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ዩናይትድ ኪንግደም በ2040 ልታስተናግድ ከምትችላቸው 70 ዋና ዋና የስፖርት ዝግጅቶች መካከል አንዱ የሆነው የሴቶች የአለም ዋንጫ መታወቁን በመንግስት የገንዘብ ድጋፍ እንደሚደረግለት ይጠበቃል ተብሏል፡፡(ሀገሬ ቴቪ)
