የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሀገራቸው ከ66 የተባበሩት መንግስታት እና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች አባልነት እንደምትወጣ ይፋ ማድረጋቸውን ተከትሎ በዓለም አቀፍ መድረክ ከፍተኛ ቁጣና ስጋት እየተቀሰቀሰ ይገኛል።
ፕሬዝዳንቱ ባስተላለፉት ውሳኔ፣ አሜሪካ ከአየር ንብረት ለውጥ፣ ከዲሞክራሲ ግንባታ እና ከሰብአዊ መብት ጥበቃ ጋር በተያያዘ የሚሰሩ ተቋማትን ድጋፍ እንደምታቆም አስታውቀዋል።
እንደ ፕሬዝዳንቱ ከሆነ፣ አሜሪካ ተሳትፎዋን የምታቋርጥባቸው ተቋማት መካከል 31ዱ የተባበሩት መንግስታት አካላት ሲሆኑ፣ ቀሪዎቹ 35ቱ ደግሞ ሌሎች ዓለም አቀፍ ስምምነቶችና ድርጅቶች ናቸው።
ከእነዚህም መካከል የመንግስታቱ የአየር ንብረት ለውጥ ፓነል (IPCC) እና የዓለም ጤና ድርጅት (WHO) በዋናነት ይጠቀሳሉ።
የዋይት ሀውስ መግለጫ እንዳመለከተው፣ ውሳኔው የተላለፈው እነዚህ ድርጅቶች “ከአሜሪካ ብሔራዊ ጥቅም ጋር ይጋጫሉ” በሚል ግምገማ ነው።
በተለይም በአየር ንብረት ስምምነቶች እና በዓለም አቀፍ የጤና ትብብር ላይ የሚታየው የአሜሪካ ሚና መቋረጥ፣ ዓለም አቀፍ ሳይንቲስቶችን እና የፖለቲካ መሪዎችን ክፉኛ አስቆጥቷል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቃል አቀባይ ስቴፋን ዱጃሪክ፣ ድርጅቱ በጉዳዩ ላይ ጥልቅ ግምገማ እያደረገ መሆኑንና አሜሪካ ከዓለም አቀፍ ትብብር መውጣቷ የሚያስከትለው ጉዳት ከፍተኛ እንደሚሆን ጠቁመዋል።
የአየር ንብረት ተመራማሪዎች በበኩላቸው፣ አሜሪካ ከIPCC መውጣቷ ዓለም ሙቀትን ለመቀነስ የምታደርገውን የጋራ ጥረት “ሽባ ያደርገዋል” ሲሉ ኮንነዋል። በተለይም የዓለም ጤና ድርጅት (WHO) ከአሜሪካ ያገኝ የነበረው 18 በመቶ የገንዘብ ድጋፍ መቋረጡ፣ እንደ ቲቢ እና ወረርሽኝ ያሉ ዓለም አቀፍ የጤና ስጋቶችን ለመቆጣጠር አስቸጋሪ እንደሚያደርገው ተነግሯል። ይህ እርምጃ አሜሪካ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ተጽዕኖ ሊቀንሰው እንደሚችል ተንታኞች እየገለጹ ይገኛሉ።
