በማይናማር በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ለማድረግ የተላከው የልዑካን ቡድን ያራዘመውን ጊዜ ጨርሶ መውጣቱም ተገለጸ
ልዑኩ ከማይናማር ሲወጣ ውክልናውን ለግብረሰናይ ድርጅቶች ሰጥቷል የተባለ ሲሆን፤ አሁንም ድብደባ እና እንግልት ከሚፈፀምበት ጣቢያ ወጥተው በታጣቂ ሀይሎች ቦታ ውስጥ የሚገኙ ከ100 በላይ ዜጎች እንዳሉ ነው የተገለጸው፡፡
ልጆቻቸው በማይናማር የታገቱባቸው ወላጆች ኮሚቴ አባል አቶ አስጨናቂ በቀለ፤ የልዕክ ቡድኑ ወደ ስፍራው ካቀናበት ጊዜ እንስቶ ባሉት 15 ቀናት ውስጥ ከ751 ዜጎች ውስጥ ከ500 በላይ የሚሆኑት ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ መደረጉን ለአሐዱ ተናግረዋል፡፡
‘ቀሪ ዜጎቹ አሁን ያሉበት ሁኔታ በፊት ከነበሩበት የተሻለ ነው’ ቢባልም ባልተመቻቸ ሁኔታ ውስጥ ያሉ ከ100 በላይ ዜጎች በዲኬቢኤ እና ቢጂኤፍ ታጣቂ ቡድኖች ጣቢያ ውስጥ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡
“ከመንግሥት በኩል ጥሩ መነሳሳቶች አሉ” ያሉት አቶ አስጨናቂ፤ “በግብረ ሰናይ ድርጅቶቹ በኩል ሥራዎች ተፋጥነው የቀሩት ዜጎች ወደ ሀገራቸው ይመለሳሉ ተብሎ ይጠበቃል” ሲሉም ገልጸዋል፡፡
በዚህ ሁሉ መሃል ግን፤ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ያሉ እና ተታለው ከገቡበት የማጭበርበር ሥራ ውስጥ እስከ አሁን ያልወጡ 42 ዜጎች መኖራቸውን ተናግረዋል::
ዜጎቹ ካሉበት አስቸጋሪ ሁኔታ እንዲወጡ መንግሥት አሁንም ያልተቋረጠ የዲፕሎማሲ ሥራውን እንዲቀጥልም የወላጆች ኮሚቴ አባሉ ጠይቀዋል፡፡
(አሐዱ ሬዲዮ)
