የ”ሹም ተምቤን” ፓርቲ ባወጣው ይፋዊ መግለጫ፤ በትግራይ ክልል ወጣቶች ላይ እየተፈጸመ ነው ያለውን ያለፍላጎት በሃይል ወደ ወታደራዊ ማሰልጠኛ የማስገባት ተግባር አጥብቆ አውግዟል።
ወጣቶች ከስራ፣ ከትምህርት ገበታቸውና ከእምነት ተቋማት ጭምር በሃይል እየታፈሱ መሆኑን የገለጸው ፓርቲው፤ ድርጊቱ መሰረታዊ የሰብዓዊ መብትና የዜጎችን ክብር የሚጥስ፣ ወጣቶችን ለከፍተኛ ፍርሃት፣ ስጋትና ስደት የሚዳርግ “ዕኩይ ተግባር” ነው ሲል ፈርጆታል።
ይህ በሕዝብና በትግል ስም የሚደረግ ቅስቀሳ ወጣቱን ለሞትና ለስቃይ የሚዳርግ፣ ሕዝብ ላልፈለገው ጦርነት በጥቂት ቡድኖች መጠቀሚያ እንዲሆን የሚደረግ ሴራ ነው ሲል ፓርቲው ከስሷል።
ድርጊቱ በትግራይ ሕዝብና በተተኪው ትውልድ ላይ ከባድ ማሕበራዊ ስቃይና ስነ ልቦናዊ ስብራት እያደረሰ እንደሚገኝና ለሰላምና ለሕዝብ መረጋጋት የማይጠቅም፣ ተጨማሪ መከራን የሚጭን መሆኑን በመግለጫው አመልክቷል።
ፓርቲው ባቀረባቸው ወሳኝ ጥሪዎች፤ የህወሓት ቡድን ይህንን አስነዋሪ ተግባር በአስቸኳይ እንዲያቆም የጠየቀ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ መንግስት ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት ተገቢውን ሕጋዊ እርምጃ እንዲወስድ አሳስቧል።
በተጨማሪም የዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች፣ የሃይማኖት ተቋማትና የሲቪክ ማሕበራት ድምጻቸውን በማሰማት ይህንን ድርጊት በይፋ እንዲያወግዙና ግፊት እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል።
