በ2018 ሩብ ዓመት የተለያዩ ተቋማት ካስወገዷቸው ንብረቶች 61 ሚሊዮን ብር ገቢ መገኘቱን የአዲስ አበባ ከተማ የመንግስት ንብረት አስተዳደር ባለስልጣን አስታወቀ።
ባለስልጣኑ «ወቅቱን የጠበቀ ንብረት አወጋገድ ለከተማችን እድገት» በሚል መሪ ሀሳብ ከባለድርሻ አካላት ጋር በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ጥቅምት 20/2018 ዓ.ም ውይይት አካሄዷል።
በውይይቱ፤ በመንግስት ተቋማት ያለአገልግሎት የተቀመጡ እና ተጠግነው አገልግሎት የማይሰጡ ንብረቶችን በማስወገድ የመንግስትን ንብረት ከብክነት መከላከል የሁሉም ተቋማት ኃላፊነት መሆኑን የባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ የሱፍ ኢብራሂም ገልጸዋል።
የባለስልጣኑ ንብረት ዘርፍ ምክትል ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ፀሐይ መንግስቱ በበኩላቸው፤ አገልግሎት የማይሰጡ ንብረቶችን ማስወገድ የከተማዋን ገቢ መደገፍ እና ምቹ የስራ አካባቢን የመፍጠር አንድ አካል መሆኑን ገልጸው፤ ንብረቶቹ በጊዜ እንዲወገዱ በማደረግ ረገድ በርካታ ስራ እየተከናወነ ይገኛል ማለታቸውን ኢፕድ ዘግቧል።።
በ2018 ተቋማት በራሳቸው እና በከተማ አስተዳደሩ የመንግስት ግዥና ንብረት ማስወገድ አገልግሎት በኩል የሚወገዱ ንብረቶች በአይነትና በብዛት ተለይተው ወደስራ መገባቱን አስታውቀዋል።
በዚህም በሩብ አመቱ ከተወገዱ ንብረቶች 61 ሚሊዮን ብር ገቢ ማግኘት መቻሉን ወ/ሮ ፀሐይ ገልጸዋል። በቀጣይም ያለአግባብ የተከማቹ ንብረቶችን በማስወገድ ገቢ ለማግኘትና ያለአግባብ የተያዘ ቦታን በማስለቀቅ ለሌላ አገልግሎት ለማዋል በትኩረት እንደሚሰራ አስገንዝበዋል ሲል ዘገባው ገልጿል።
