ከአንባቢያን ዘንድ በሚቀርቡ ጥያቄዎች መሠረት መጽሐፍትን ከውጪ ሀገራት ገዝቶ ለማስገባት የውጭ ምንዛሬ እጥረት ተግዳሮት እንደሆነበት፤ የብሔራዊ ቤተ መጻሕፍትና ቤተ መዛግብት አገልግሎት (ወመዘክር) አስታውቋል፡፡
በቀን ከ3 ሺሕ ለሚሆኑ አንባቢያን አገልሎት እየሰጠ እንደሚገኝ የገለጸው አገልግሎቱ፤ በአንባቢያን ጥያቄ ከሚቀርቡት መጽሐፍት መካካል በቴክኖሎጂ ላይ ያተኮሩ፣ የታሪክ ይዘት ያላቸው እና ለትምህርት አጋዥ የሆኑ መጽሐፍት እንደሚገኙበት ተናግሯል፡፡
በአገልግሎቱ የባህረጥበባት አገልግሎት ሰጪ የሆኑት ወይዘሮ አለም ጌታቸው፤ በዓመት ከ500 በላይ የሚሆኑ መጽሐፍትን ከውጭ ሀገራት ወደ ሀገር ውስጥ በግዢ መልክ ማስገባት እንደሚያስፈልግ ለአሐዱ ተናግረዋል፡፡
በቤተ መጻሕፍትና ቤተ መዛግብት አገልግሎት (ወመዘክር) በተለያዩ ጉዮች ላይ ትኩረታችን ያደረጉ መጽሐፍት ለአንባቢያን እየቀረቡ እንደሚገኝ የገለጹም ሲሆን፤ በአንባቢያን ዘንድ በተጨማሪነት ለንባብ የሚጠየቁ መጽሐፍት ስለመኖራቸው አስረድተዋል፡፡
ከአንባቢያን ዘንድ የመጽሐፍት ጥያቄ ሲቀርብ ከውጭ ወደ ሀገር በግዢ እንዲገባ የሚደረግበት አሰራር ስለመኖሩ በመግለጽም፤ በአንባቢያን የሚጠየቁ መጽሐፍትን ለማሟላት በውጭ ምንዛሬ እጥረት ምክንያት ማሳካት እንዳልተቻለ ገልጸዋል፡፡
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የአንባቢያን ቁጥር እየጨመረ እንደሚገኝ የገለጹም ሲሆን፤ ለአንባቢያን በተሟላ መልኩ መጽሐፍትን ለማቅረብ ጥረቶችን እየተደረጉ ስለመሆኑም ተናግረዋል፡፡
አክለውም በመጽሐፍት ልውውጥ፣ በስጦታ እንዲሁም በግዢ መጽሐፍትን ለአንባቢያን የሚያቀርብበት ሁኔታ ስለመኖሩ ገልጸው፤ በአሁኑ ሰዓት በአብዛኛው መጽሐፍትን እያገኙ ያሉት ከተለያዩ ሰዎች በስጦታ መልክ ከሚሰጣቸው እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
በተጨማሪም “የብሔራዊ ቤተ መጻሕፍትና ቤተ መዛግብት አገልግሎት (ወመዘክር) ሕንጻ ከተጠናቀቀ በኋላ፤ ከዚህ ቀደም ይስተዋል የነበርው የአንባቢያን መቀጨናነቅ ቀንሷል” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡
ሐምሌ 10/2017 (አሐዱ ሬዲዮ)
