ቱርክ በአፍሪካ ቀንድ “አዲስ ግጭቶች” “በፍጹም” ማየት እንደማትፈልግ እና በቀጠናው “በስቃይ ውስጥ በሚገኙ” ሰዎች ላይ “አዲስ ህመም” መጨመር እንደማይገባ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ረቺብ ጣይብ ኤርዶኻን ተናገሩ።
የአፍሪካ ቀንድ የውጭ ኃይሎች “የመፋለሚያ ሜዳ” ሊሆን እንደማይገባም ፕሬዝዳንቱ አሳስበዋል።
የቱርኩ ፕሬዝዳንት ማሳሰቢያውን የሰጡት፤ ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ጋር በሰጡት የጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነው።
ኤርዶኻን
ከ10 ዓመት በኋላ በኢትዮጵያ ጉብኝት ለማድረግ አዲስ አበባ የገቡት፤ ዛሬ ማክሰኞ የካቲት 10፤ 2018 እኩለ ቀን ላይ ነበር።
በኢትዮጵያ በኩል ከፍተኛ ግምት የተሰጠው የቱርኩ ፕሬዝዳንት ጉብኝት አቀባበል እና ጋዜጣዊ መግለጫ፤ በብሔራዊው ቴሌቪዥን በቀጥታ ተላልፏል። ኤርዶኻን ሰባት ደቂቃ በፈጀው የተጻፈ ንግግራቸው ካነሷቸው ጉዳዮች መካከል የአፍሪካ ቀንድ ሰሞነኛ የፖለቲካ ሁኔታ ይገኝበታል።
“የዓለም ሁሉ አይን በአፍሪካ ቀንድ ላይ ባረፈበት በዚህ ጊዜ፤ የኢትዮጵያ ረጅም ዘመናት ያስቆጠረ የሀገረ መንግስት መዋቅር እና ተምሳሌታዊ አስተዳደር የበለጠ አስፈላጊ እየሆነ መጥቷል” ያሉት ፕሬዝዳንት ኤርዶኻን፤ በአፍሪካ ቀንድ ላይ ቱርክ ያላትን አቋም አያይዘው ግልጽ አድርገዋል።
“ኢትዮጵያ በምትገኝበት ቀጠና ያሉ ሀገራት ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት አስፈላጊነት ላይ፤ ያለንን አቋም በተለይ አጽንኦት መሰጠት እፈልጋለሁ” ብለዋል የቱርኩ ፕሬዝዳንት።
ኢትዮጵያ ኢንሳይደር
