በቻይና ሺያመን በተካሄደው የዳይመንድ ሊግ የወንዶች 5000 ሜትር ሩጫ ውድድር ኢትዮጵያዊው አትሌት ይሁኔ አዲሱ 12፡57.32 በሆነ አስደናቂ ሰዓት አንደኛ በመውጣት አሸንፏል።
አትሌቱ ያስመዘገበው ይህ ውጤት የዓመቱ የዓለማችን ፈጣኑ ሰዓት ከመሆኑም በላይ የውድድሩ አዲስ ክብረ ወሰን ሆኖ ተመዝግቧል።
በዚሁ እጅግ አጓጊ ውድድር ላይ ሌሎች ኢትዮጵያውያን አትሌቶችም ድሉን ያደመቁ ሲሆን፣ አብዲላሂ መሀመድ በ12፡57.90 ሁለተኛ እንዲሁም ቢኒያም መሀሪ በ12፡58.51 ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ የድሉን መድረክ ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያ ባንዲራ አሸብርቀውታል።
በሌላ በኩል ከፍተኛ ግምት ተሰጥቷቸው የነበሩት የኬንያ አትሌቶች በውድድሩ ላይ ጠንካራ ፉክክር ቢያደርጉም ያሰቡትን ውጤት ሳያሳኩ ቀርተዋል።
ኤድዊን ኩርጋት ውድድሩን በ5ኛ ደረጃ ሲያጠናቅቅ፣ ከ2020 ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በዚህ ርቀት የተወዳደረው ታዋቂው አትሌት ጢሞቲ ቼሩዮት ግን ሳይሳካለት ቀርቶ በ12ኛ ደረጃ ለማጠናቀቅ ተገዷል።
