ኢትዮ ቴሌኮም ከአዲስ አበባ ውጪ ለመጀመሪያ ግዜ በአዳማ ከተማ አራተኛ የኤሌትሪክ መኪና ቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያ በይፉ አስጀመረ።
እያደገ የመጣውን የኢትዮጵያን የኤሌክትሪክ መኪና ስነ-ምህዳር በስማርት ቴክኖሎጂ ለመደገፍ በዛሬው ዕለት ለመጀመሪያ ጊዜ ከአዲስ አበባ ውጪ፣ በአዳማ ከተማ የገነባውን አራተኛውን ፈጣን የኤሌክትሪክ መኪና ቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያ በይፋ አስጀምሯል።
በአራተኛው ምዕራፍ ተጠናቆ ወደ ሥራ የገባው ይህ ጣቢያ፤ በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) የላቀ ቴክኖሎጂን ይጠቀማል።
የአውሮፓ ስሪት ለሆኑ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ጭምር አገልግሎት መስጠት የሚያስችል አቅም ያለውና ከተሽከርካሪዎቹ ዓይነት ጋር ራሱን የሚያጣጥም ፈጣን ኃይል መሙያ የተገጠመለት ነው።
የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ኃይል መሙያ ጣቢያው በአንድ ጊዜ እስከ 12 ተሽከርካሪዎች የማስተናገድ አቅም ያለው በመሆኑ ለአሽከርካሪዎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል ነውም ተብሏል።
ኢቲዮ ቴሌኮም ቀደም ሲል የገነባቸውን ሦስት ጣቢያዎች ጨምሮ በአጠቃላይ በአንድ ጊዜ ለ60 የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች አገልግሎት መስጠት የሚችልበትን አቅም የሚያሳድግ እንደሆነ ተገልጿል።
በቀጣይም ለአካባቢ ጥበቃ ተስማሚ የሆኑ የትራንስፖርት አማራጮችን በዲጂታል መፍትሄዎች በመደገፍ፣ የካርቦን ልቀትን ለመቀነስ እንዲሁም የሀገራችንን የአረንጓዴ ቴክኖሎጂ ሽግግር በማፋጠን ዘላቂና ብሩህ መጻኢ ዕድልን ለመገንባት ያለውን ራዕይ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተቋሙ አስታውቋል።
በተጨማሪም ኢትዮ ቴሌኮም 130ኛ ዓመት ክብረ-በዓሉን ምክንያት በማድረግ ባዘጋጀው የኢትዮ 130 ሜጋ ፕሮሞ እና ኢትዮ 131 ላኪ ስሎት የሽልማት መርሃ ግብር በዛሬው ዕለትም ዕጣ ለወጣላቸው የአዲስ አበባ፣ ድሬዳዋ፣ ጅማ እና የአሶሳ ባለዕድለኞች፣ ሦስት ዘመናዊ ቮልስዋገን (ID.4)፣ ሁለት የቢ.ዋይ.ዲ (BYD) እና አንድ ቶዮታ (BZ3x) የኤሌክትሪክ መኪኖችን የተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት ቁልፍ አስረክቧል፡፡
