በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ነገ ቅዳሜ ፓኪስታን ዋና ከተማ ኢስላማበድ ውስጥ ንግግር ይጀመራል ተብሎ እየተጠበቀ ባለበት በአሁኑ ጊዜ ሊባኖስ ውስጥ ተኩስ አቁም ሳይደረግ ድርድር እንደማይጀመር ኢራን ገለጸች።
በኢራን መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ተሰሚነት ያላቸው አገሪቱ ፓርላማ አፈ ጉባኤ ሞሐማድ ባጌር ጋሊባፍ እንዳሉት ከአሜሪካ ጋር የሚካሄደው ድርድር የሚጀመረው ሁለት ቁልፍ ቅድመ ሁኔታዎች ሲሟሉ ብቻ ነው።
አፈ ጉባኤው ወሳኝ ያሏቸው የድርድሩ ቅድመ ሁኔታዎች እስራኤል በሊባኖስ ውስጥ የምታካሂደውን ወታደራዊ ጥቃት የሚያስቆም ተኩስ አቁም እና እንዳይንቀሳቀስ የታገደው የኢራን ሀብት መለቀቅ ናቸው።
ጋሊባፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ እንዳሉት እነዚህ ሁለት እርምጃዎች አሜሪካ እና ኢራን ከሁሉ በፊት ተግባራዊ እንዲሆኑ የተስማሙባቸው መሆቸወውን አመልክተዋል።
ሁለቱ ነጥቦች “ድርድሩ ከመጀመሩ በፊት ሊፈጸሙ የሚገቡ ናቸው” በማለት ቅድመ ሁኔዎች መሆቸወውንም አፈ ጉባኤው ገልጸዋል።
አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት እንደከፈቱ እስራኤል በሌላ በኩል የኢራን አጋር በሆነው የሊባኖሱ ታጣቂ ቡድን ላይ ከፍተኛ ጥቃት እያካሄደች ሲሆን፣ ከኢራን ጋር የተኩስ አቁም ከተደረገ በኋላም ዘመቻዋን አጠናክራ ቀጥላለች።
በርካታ የኢራን ባለሥልጣናት በሊባኖስም ተኩስ አቁሙ ተግባራዊ እንዲሆን እየጠየቁ ሲሆን፣ አሁን አፈ ጉባኤው የሰነዘሩት አስተያየት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚደረገውን ድርድር እንዳያጨናግፈው ተሰግቷል።
BBC
