ማህበሩ “ቢንጎ” በሚል ስያሜ የጀመረው ይህ ፕሮጀክት ሴቶችን በራሳቸው አገዛዝ (በራስ አገዝ) በማደራጀት፣ ችግር ያለባቸውን እንዲሁም ከተለያዩ የአረብ ሀገራት የተመለሱ እናቶችን እና ሴቶችን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለማድረግ ያለመ እንደሆነ ተብራርቷል።
ፕሮጀክቱ ሴቶች የፋይናንስ ነፃነት እንዲያገኙ እና ኑሯቸውን እንዲያሻሽሉ ትልቅ ድጋፍ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል።
የወወክማ የፕሮግራም ክፍል ዳይሬክተር ወ/ሮ ሄለን ተፈራ ከጣቢያችን ጋር በነበራቸው ቆይታ እንዳመለከቱት፤ድጋፉ ሴቶች ለ8 ቀናት የሚሆን ስልጠና እንዲወስዱ የሚያስችል ሲሆን፤ ከተለያዩ የፋይናንስ ተቋማት ጋር በመተባበር ሥራ የጀመሩትን እንዲቀጥሉ በፋይናንስ የሚረዳ ነው።
ይህም ሴቶቹ የጀመሯቸውን የሥራ ዘርፎች እንዲያጠናክሩ እና የገቢ ምንጫቸውን እንዲያሰፉ ያስችላቸዋል።
ፕሮጀክቱ በአድዋ፣ አክሱም፣ ሃዋሳ፣ ደብረ ማርቆስ እና አዲስ አበባ የሚተገበር ሲሆን፣ ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ እንደሆነም ተገልጿል።
የእነዚህ ፕሮጀክቶች መተግበር ሴቶችን ከኢኮኖሚያዊ ጥገኝነት በማላቀቅ፣ በራስ መተማመን እና በማህበረሰቡ ውስጥ ያላቸውን ሚና ከፍ ለማድረግ ጉልህ አስተዋፅዖ እንዳለውም ተመላክቷል።
ወወክማ በአሁኑ ወቅት ወጣቶችን፣ ክርስቲያኖችን እና ሴቶችን በማብቃት እና በመደገፍ ረገድ የሚሠራ ሲሆን፤ ከ75 ዓመት በላይ አገልግሎት መስጠቱም ይታወቃል።
