የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በተመለከተ በአለም አቀፉ ማህበረሰብ ዘንድ ሲንጸባረቁ የነበሩ የተሳሳቱ ትርክቶችን በሳይንሳዊ መረጃ ለማረም ከተመረጡ አምስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በጋራ እየሰራ መሆኑን አስታውቋል።
የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ዶ/ር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ አሐዱ ላቀረበላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሲሰጡ ፤ ኢትዮጵያ በግድቡ ጉዳይ ላይ እውነትን ይዛ ሳለች አለም አቀፉ ማህበረሰብ እና ሚዲያው ግን የሌሎች ሀገራትን የውሸት ትርክት እንደ እውነት ሲቀበል ቆይቷል ብለዋል።
ለዚህም እንደ ዋነኛ ምክንያት ያነሱት በኢትዮጵያ በኩል የነበረውን በመረጃ ላይ የተመሰረተ የትንታኔ እጥረት ነው።
ሚኒስትሩ አክለውም አጠቃላይ ሳይንሳዊው ማህበረሰብ በሳይንስ ቋንቋ እንዲያወራ ማድረግ ይቀረናል ያሉ ሲሆን ፤ በድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ዙሪያ የነበረንን ሀሳብ አለም አቀፉ ማህበረሰብ ሊረዳው በሚችለው መንገድ አለማስረዳታችንን በር ዘግቶ እንደመጮህ ይቆጠራል ብለውታል።
እነዚህን የመረጃ እና የተግባቦት ክፍተቶች ለመድፈን ፤ የመንግስት ተቋማት ብቻቸውን በቂ ባለመሆናቸው ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ያሳተፈ አዲስ ስትራቴጂ ተነድፎ ወደ ስራ መገባቱን ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
በዚህም መሰረት አዲስ አበባ ፣ ባህር ዳር ፣ አርባ ምንጭ ፣ ጅማ እና አዲስ አበባ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በልዩ ሁኔታ ተለይተው በጋራ መስራት ጀምረዋልም ብለዋል።
ትኩረታቸውን በህዳሴው ግድብ ፣ በአባይ ወንዝ እንዲሁም በግብጽ እና ሱዳን ነባራዊ ሁኔታዎች ላይ በማድረግ ጥልቅ የምርምር ስራዎችን እና የትንታኔ ጽሑፎችን በማዘጋጀት ላይ እንደሚገኙ የገለጹት ሚኒስትሩ ተቋማቱ የሚያዘጋጇቸው ሳይንሳዊ ምርምሮች በየአመቱ ቢያንስ ሁለት ጊዜ እንዲታተሙ እየተደረገ ሲሆን ይህም የኢትዮጵያን እውነት በሳይንስ አስደግፎ ለአለም በማሳወቅ ረገድ አመርቂ ውጤቶች እያመጣ እንደሆነ ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት የግንባታ ስራው ተጠናቆ ሀይል ማመንጨት የጀመረው የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የመሰረት ድንጋይ የተቀመጠው ከ 15 አመታት በፊት መጋቢት 24 ቀን 2003 አ/ም እንደነበር ይታወሳል።
