የማርበርግ ቫይረስ በሀገሪቱ ለመጀመሪያ ጊዜ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጅንካ ከተማ ከተከሰተበት ጀምሮ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 10 የደረሰ ሲሆን ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ በዚሁ በሽታ የ5 ሠዎች ህይወት አልፏል።
በጤና ሚኒስቴር የማርበርግ ቫይረስ አማካሪ እንዲሁም የድንገተኛ እና ፅኑ ህክምና ተባባሪ ፕሮፌሰር ዶክተር ወልደሰንበት ዋጋነው፣ በሽታው በቫይረስ የሚዛመት እና ከኢቦላ ጋር ተመሳሳይነት እንዳለው አስታውቀዋል።
ቫይረሱ ከኮቪድ 19 ወረርሽኝ ጋር ግንኙነት እንደሌለው ገልጸው፣ ከሌሎች ቫይረሶች በተለየ መልኩ በፍጥነት ምልክት እንደሚያሳይ ተናግረዋል።
ቫይረሱ በሽታ የመቋቋም አቅምን የሚያዳክም እንዲሁም ያለ ምክንያት የሰውነት መድማት የሚያስከትል መሆኑን ገልጸው፣ እስካሁን በሳይንስ የተረጋገጠ መድሐኒት ባይኖረውም በአፍሪካ እና በሌሎችም ሀገራት ጥቅም ላይ ውለው ለውጥ ያሳዩ መድሀኒቶች ወደ ሀገር ውስጥ እየገቡ መሆኑን ገልጸዋል።
ከዚህም በተጨማሪ በሙከራ ላይ ያሉ ክትባቶች መኖራቸውን አስታውቀዋል።
በበሽታው የተያዘ ታማሚ ሙሉ ለሙሉ እገዛ የሚፈልግ በመሆኑ እገዛ ከተደረገለት፣ ከሞት የመትረፍ እድል እንዳለው የሌሎች ሀገራትን ተሞክሮ በማንሳት ያብራራሉ።
ዶክተር ወልደሰንበት ቫይረሱ በወንድ ዘር ፈሳሽ እና በአይን ውስጥ ብቻ እስከ 1 ዓመት መቆየት እንደሚችል ገልጸዋል። በእነዚህ የሰውነት ክፍሎች በሽታ የመከላከል አቅም ዝቅተኛ በመሆኑ ቫይረሱ የመቆየት እድል እንዳለው ነው ያብራሩት።
በደም እና የአይን ብሌን ልገሳ አማካኝነትም እንደሚተላለፍ አስታውቀዋል።
በአእዋፋት እና በሰዎች እንቅስቃሴ አማካይነት በድንበሮች አካባቢ በስፋት እንደሚሰራጭ ያስታወቁት ባለሙያው፤ በተጠናከረ ሁኔታ ቁጥጥር ማድረግ ይገባልም ብለዋል።
ከዚህ በኃላም የሚከሰቱ ቫይረሶች ሊኖሩ እንደሚችሉ ስጋታቸውን በመግለጽ አስፈላጊው ጥንቃቄ እንዲደረግ አሳስበዋል።
(መናኸሪያ ሬዲዮ)
