በሪል ስቴት ዘርፉ ያለዉን የተጋነነ ዋጋ በመቀነስ በመካካለኛና በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ያሉ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ለማድረግ መንግስት የመሬት አቅርቦት ችግርን የመፍታት፣
ከቤት ልማት ጋር የተያያዙ ታክሶችን የመቀነስና የፋይናንስ አማራጮችን የማቅረብ ስራዎች መስራት እንዳለበት የማህበሩ የሒሳብ ኃላፊ ደበበ ሰይፉ ለአራዳ ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሪል ስቴት አልሚዎች ማህበር ከዚህ በፊት በዘርፉ በተናጥል ለሚከሰቱ ችግሮች በጋራ መፍትሔ ለመስጠት መቋቋሙን አስረድተዋል፡፡
እንዲሁም ማህበሩ የቤት አልሚዎችን፣ ቤት ፈላጊዎችንና መንግስትን በአንድ መድረክ በማሰባሰብ በዘርፉ ያለዉን እንቅስቃሴ ጤናማ ለማድረግ እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡
ማህበሩ የራሱን ህግ አውጥቶ ከመስራት ባሻገር እየጨመረ የመጣውን የቤት ፈላጊዎች ቁጥር ፍትሐዊ በሆነ መልኩ ለመመለስ እንደሚሰራ የገለጹት ደግሞ የማህበሩ ፕሬዝዳንት አቶ አለማየሁ ከተማ ናቸዉ፡፡
በዘርፉ ያለዉን የተጋነነ የዋጋ ሁኔታ ለማስተካከል መንግስት የተለያዩ የግንባታ ምርቶች ሀገር ዉስጥ እንዲመረቱ እገዛ እንዲያደርግ ማህበሩ ጫና የመፍጠር ስራ እየሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡
ማህበሩ የፊታችን ቅዳሜ ሰኔ 7 ቀን 2017 ዓ.ም የመጀመሪያ ጉባዔውን እንደሚያካሂድም አስታዉቋል፡፡
(አራዳ ኤፍ ኤም)
