ከ2010 ዓ.ም ጀምሮ የብቃት ማረጋገጫ ፈተና ሳይፈተኑ ዲግሪ በያዙ ተማሪዎች ጉዳይ ላይ የመንግሥት ውሳኔ እንዲሰጥ እየተጠበቀ መሆኑን የኢፌድሪ ትምህርትና ስልጠና ባለስልጣን ገልጿል።
ባለስልጣኑ ማንኛውም አካል ሕጋዊ እውቅና ካለው የከፍተኛ የትምህርት ተቋም ትምህርቱን ሲያጠናቅቅ የትምህርት ማስረጃውን የማረጋገጥ ሥራ እንደሚሰራ ይታወቃል።
በዚህም መሠረት ባለስልጣን መ/ቤቱ የዲፕሎማ ትምህርታቸውን እና የብቃት ማረጋገጫ ምዘናቸውን ሳያጠናቅቁ ዲግሪ የያዙ ተማሪዎችን ማረጋገጫ ለመስጠት የመንግሥት ውሳኔን የሚፈልግ መሆኑን አስታውቋል።
የባለስልጣኑ የተቋማት ቁጥጥር ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቢኒያም ኤሮ እንደገለጹት ከ2010 ዓ.ም ጀምሮ ዲግሪ ያለው አካል ማረጋገጫ እንዲያገኝ የብቃት ማረጋገጫ ያለፈበትን ማስረጃ ይዞ መቅረብ አለበት።
ማንኛውም ሰው የዲግሪ መርሃ ግብሩን ከመቀጠሉ በፊት ምዘናውን ማጠናቀቅ ቢኖርበትም፤ አሁን ወደ ተቋሙ የሚመጡ ማረጋገጫ ፈላጊዎች ዘግይተው ምዘናውን የወሰዱ እና የብቃት ማረጋገጫ ምዘና ያልወሰዱ መሆናቸውን ገልጸዋል።
ስለሆነም ይህን ጉዳይ ለመፍታት መንግሥት ውሳኔ እንዲሰጥበት የመፍትሔ ሀሳቦችን እያቀረቡ መሆኑን አንስተዋል።
እንደ ሀገር ባለው መመሪያ መሠረት፤ እስከ 2010 ዓ.ም ድረስ ባለው ጊዜ ዲግሪያቸውን ያገኙ ተማሪዎች ክፍት መደረጉና ማረጋገጫ የሚሰጥ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።
ለዚህም በተለያዩ ክልሎች በተለያየ መልኩ የትምህርት ማስረጃዎችና የሲኦሲ ምዘናዎች በመኖራቸው መሆኑን ጠቁመዋል።
ይህም አሁን ላይ በስፋት እየገጠመ ያለ ችግር መሆኑንም አንስተው፤ “ዲፕሎማውን ተምሮ ዲግሪ ለመቀጠል የሚፈልግ ሰው በቅድሚያ የሲኦሲ ምዘናውን ማጠናቀቅ አለበት” ሲሉ አሳስበዋል።
(አሐዱ ሬድዮ)
