የአዲስ አበባ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት፤ በመዲናዋ በቂርቆስ ክ/ከተማ ወረዳ 7 የሚገኘው የተውፊቅ (ፍል ውሃ) መስጂድ ግንባታ በሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ “ሙሉ ወጪ” የፊታችን ሰኞ ይጀመራል ሲል ጁመዓ ጥቅምት 14/2018 አስታውቋል። ምክር ቤቱ ግንባታው የሚጠናቀቅበትን ጊዜ አልገለፀም።
እንደ ምክር ቤቱ መረጃ ከሆነ፣ ግንባታው የሚጀመረው መስጂዱን “በተሻለ መልኩ ለመገንባት” በአዲስ አበባ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ም/ቤት እና በሚድሮክ ኢንቬስትመንት ግሩፕ መካከል ከዚህ ቀደም በተደረሰ ስምምነት መሠረት ነው። መስጂዱ “ውብ፣ የሙስሊሙን እሴት የሚናገር፤ ሁለንተናዊ አገልግሎት የሚሰጥ” ተደርጎ ይገነባል ተብሏል።
ግንባታውን ለማስጀመር የምክር ቤቱ ፕሬዝዳንት ሸይኽ ሡልጣን አማንን ጨምሮ የእስላማዊ ተቋማት ዘርፍ ተጠሪ ኡስታዝ አዩብ ደርባቸው፣ ከሚድሮክ ኢንቬስትመንት ግሩፕ ደግሞ አቶ ጀማል አሕመድና ሌሎችም መገኘታቸው ተገልጿል። በ1978 የተመሠረተው የፍል ውሃ መስጂድ አዲስ ግንባታ የማጠናቀቂያ ጊዜ በመረጃው አልተጠቀሰም።
(ሚንበር ቲቪ)
