በኢትዮጵያ ልማት ባንክ (DBE) ከፍተኛ ሹመቶች እና በአመራር ምደባ ዙሪያ የተነሳ አለመግባባትን ተከትሎ፣ የባንኩ ከፍተኛ አመራር በአዲስ መልክ ተዋቅሯል።
ዶ/ር ኢሣያስ ካሣ ፕሬዝዳንት ሆነው የተሾሙ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ (EIH) ዋና ሥራ አስፈጻሚ የሆኑት ዶ/ር ብሩክ ታዬ ደግሞ የቦርዱ ሰብሳቢ ሆነው ተሰይመዋል።
ባየው መግለጫ እና የውስጥ ደብዳቤ ላይ ዶ/ር ብሩክ የአመራር ለውጡን ያደረጉት “ተቋማዊ ውጤታማነትን ለማስመለስ እና የልማት ባንኩን ከብሔራዊ ልማት ቅድሚያዎች ጋር ለማጣጣም ያለመ ሰፊ የማሻሻያ አጀንዳ” አካል መሆኑን ገልጸዋል።
የቀድሞ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ተክለወልድ አጥናፉ እና ፕሬዝዳንት የነበሩት ዶ/ር እመቤት መለሰ (ዓርብ፣ ታኅሣሥ 3 ቀን 2018 ዓ.ም.) የተተኩት፣ በምክትል ፕሬዝዳንቶች ሹመት እና ለከፍተኛ ሠራተኞች የብቃት ፈተና አሰጣጥ ዙሪያ በቦርዱ እና በዋና ሥራ አስፈጻሚው መካከል የነበረው አለመግባባት ከጠነከረ በኋላ ነው።
ጉዳዩን በቅርበት የሚያውቁ ሰዎች እንደሚሉት ከሆነ፣ ይህ የተካረረ ልዩነት ስትራቴጂያዊ የውሳኔ አሰጣጥን እያደናቀፈ ነበር።
ለባንኩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች እንዳሉት፣ አለመግባባቱን ለማርገብ የመጨረሻ ጥረት የተደረገው ከአንድ ሳምንት በፊት ሲሆን፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሚኒስትር ወ/ሮ አለምፀሐይ ጳውሎስ እና የማዕከላዊ ባንክ ገዥ ዶ/ር እዮብ ተካልኝ በአቶ ተክለወልድ እና በዶ/ር እመቤት መካከል ስብሰባ ጠርተው ነበር። ሆኖም ውይይቱ ልዩነቱን ማጥበብ እንዳልቻለ ምንጮቹ ገልጸዋል።
ዶ/ር ኢሣያስ ካሣ የካፒታል ገበያ ባለሥልጣን (ECMA) ሲመሠረት በዶ/ር ብሩክ ይመራ የነበረው መስራች ሥራ አስፈፃሚ አካል ውስጥ ነበሩ። የዶክትሬት ዲግሪያቸውን የተከታተሉት ደግሞ በአሜሪካ ዋልደን ዩኒቨርሲቲ ነው።
ከ2010 እስከ 2011 ዓ.ም. በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ሆነው አገልግለዋል። በተጨማሪም በኢንተለጀንስ እና ደህንነት መረጃ መረብ ኤጀንሲ (INSA) የስትራቴጂ እና የሳይበር ምርምር ዳይሬክተር እንዲሁም የሕግ አማካሪ ሆነው አገልግለዋል።
ፎርቹን ጋዜጣ
