የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር በአዳራሽ ኪራይ ላይ ያደረገው ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ፣ ቴአትር አዘጋጅ ኢንተርፕራይዞችንና ባለሙያዎችን ከዘርፉ እያራቃቸው መሆኑን ቅሬታ አቅራቢዎች ገለጹ።
ፕሮዲውሰሮች ለደራሲ፣ ለአዘጋጅና ለተዋንያን ከሚከፍሉት ክፍያ በተጨማሪ የቲኬት ቀረጥና የመንግሥት ግብር የሚጠብቃቸው በመሆኑ፣ አዲሱ የኪራይ ዋጋ ፕሮዲውሰሮችን ከገበያ የሚያስወጣ ነው ተብሏል።
ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የኢንተርፕራይዝ ባለቤቶችም የኪራይ ዋጋው በድንገት ከሦስት እጥፍ በላይ መጨመሩ በስራቸው ላይ ከፍተኛ ስጋት እንደፈጠረባቸው ገልጸዋል።
ባለፉት ዓመታት የቴአትር ሥራ አዋጭ ባለመሆኑ ሁለት መቶ ያህል ኢንተርፕራይዞች ሙያውን ትተው ወጥተዋል፡፡ አሁን የቀሩት ከሁለትና ከሦስት የማይበልጡ ኢንተርፕራይዞችም በአዳራሽ ኪራይ ዋጋ መጨመርና በሌሎች ገፊ ምክንያቶች ከሥራው ለመውጣት በመገደድ ላይ ናቸው ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር፣ የቴአትር መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ካሌብ ዋለልኝ እንደተናገሩት፣ የቴአትር አዳራሽ ኪራይ ዋጋን በተመለከተ ጥናት ላይ ተመሥርቶ ጭማሪ እንዲደረግ የተወሰነው ከሦስት ዓመታት በፊት ነበር ብለዋል፡፡ሆኖም በቅርቡ ፀድቆ ወደ ተግባር እንዲገባ መደረጉ ከጊዜው ጋር ሊጣጣምና መልስ ሊሆን የማይችል ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡
በዋጋ ጭማሪውም ከኢንተርፕራይዞችና ከቴአትር ፕሮዲዩሰሮች ለቴአትር ቤቱ ቅሬታ እየቀረበ መሆኑን፣ ችግሩ በጥናት ተለይቶ ማስተካከያ ማድረግ የሚያስፈልግ ከሆነ ቴአትር ቤቱ ማስተካከያ ከማድረግ ወደኋላ እንደማይል አቶ ካሌብ አስታውቀዋል፡፡
ሪፖርተር ጋዜጣ
