በግንባታ ላይ የሚገኘውን የኒያ ኦቲዝም ማዕከል መጠለያ ሕንጻ ለአገልግሎት ለማብቃት 100 ሺሕ ሰዎች እያንዳንዳቸው 300 ብር በማዋጣት የሚሳተፉበት ታላቅ የንቅናቄ ጥሪ ቀረበ።
ከሚያዝያ 6 እስከ ግንቦት 1 ቀን 2018 ዓ.ም. የሚቆየው ይህ ዘመቻ፣ መዋቅራዊ ግንባታው ተጠናቅቆ በፊኒሺንግ ስራ ላይ የሚገኘውን ሕንጻ በፍጥነት ለማጠናቀቅ ያለመ ነው።
የማዕከሉ ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ እሌኒ ዳምጠው እንደገለጹት፣ ይህ ፕሮጀክት መሳካቱ ለማዕከሉ መስራችና ለዘርፉ ባለውለታ ለነበረችው ለሟቿ ዘሚ የኑስ ትልቅ መታሰቢያ የሚሆን ነው።
ይህ የገቢ ማሰባሰቢያ ንቅናቄ በኢትዮጵያ ለ24ኛ ጊዜ የሚከበረውን የኦቲዝም ቀን በማሰብ የተዘጋጀ ሲሆን፣ ህብረተሰቡ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ ተላልፏል።
ማንኛውም በጎ አድራጊ ግለሰብ 9616 አጭር የጽሑፍ መልዕክት ቁጥርን በመጠቀም የገንዘብ ድጋፍ ማድረግ የሚችል ሲሆን፤ የ100 ሺሕ ሰዎች መረባረብ የኦቲዝም ሕጻናትን ተጠቃሚ የሚያደርገውን ይህን ግዙፍ ሕንጻ ለአገልግሎት ዝግጁ ለማድረግ ወሳኝ ሚና ይጫወታል።
