የገቢ መሰብሰብ አቅምን ማሳደግ ላይ ያተኮረ ቀጣናዊ ኮንፍረንስ ከዛሬ ጀምሮ በአዲስ አበባ ይካሄዳል
የሀገር ውስጥ ገቢ የመሰብሰብ አቅም ማሳደግ ላይ ያተኮረ ቀጣናዊ ኮንፍረንስ ከዛሬ ጀምሮ ለተከታታይ አራት ቀናት በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ የገቢዎች ሚኒስቴር አስታውቋል።
ኮንፍረንሱ “የልማት ግቦችን ለመደገፍ የሀገር ውስጥ ገቢ አሰባሰብን ማጎልበት” በሚል መሪ ሀሳብ እንደሚካሄድም ተጠቁሟል።
ኮንፍረንሱን የገቢዎች ሚኒስቴር፣ የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት(አይኤምኤፍ) እና የአይኤምኤፍ ቀጣናዊ የቴክኒክ ድጋፍ ማዕከል የምስራቅ አፍሪካ ቢሮ(አፍሪታክ) በጋራ አዘጋጅተውታል።
በኮንፍረንሱ ላይ የኢትዮጵያ ገቢዎች ሚኒስቴር እና የገንዘብ ሚኒስቴር ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችን ጨምሮ ከ11 የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት የተወከሉ የዘርፉ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣ የገቢና ፋይናንስ ባለሙያዎችና አማካሪዎች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት እንደሚገኙም በመረጃው ተመላክቷል።
የልማት ግቦችን መደገፍ የሚያስችልና የሀገር ውስጥ ገቢ አሰባሰብን ማጎልበት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መምከር የከንፍረንሱ ዋና ዓላማ መሆኑም እንዲሁ።
ቀጣናዊ ኮንፍረንሱ እስከ መጋቢት 5 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚቆይ እና ከሁነቱ ጎን ለጎን የተሳታፊዎች የጉብኝት መርሃ ግብር መዘጋጀቱን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመለክታል።
