የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁ ለኢራን ህዝብ ባስተላለፉት ያልተለመደና ቀጥተኛ መልዕክት፣ በሀገሪቱ ላይ ለዓመታት የቆየውን የአያቶላህ አገዛዝ እንዲያስወግዱ ጥሪ አቀረቡ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኤክስ (X) ገጻቸው ባሰፈሩት ሐሳብ፣ አሁን ያለው ሁኔታ የኢራን መንግስትን ለመገርሰስ “በሕይወት ዘመን አንድ ጊዜ የሚገኝ ዕድል” መሆኑን በመጥቀስ፣ ኢራናውያን ዕድሉን ተጠቅመው ለለውጥ እንዲነሱ አሳስበዋል።
ኔታንያሁ አክለውም “ጦርነቱን እንቋጨዋለን” በማለት እስራኤል የጀመረችውን ወታደራዊ እርምጃ አጠናክራ እንደምትቀጥል ፍንጭ ሰጥተዋል።
በሌላ በኩል ቴህራን ለዚህ ጥሪ የሰጠችው ምላሽ የከረረ ሆኗል።
የኢራን የፖሊስ አዛዥ ማንኛውንም ዓይነት ፀረ-መንግስት ተቃውሞ እንዳይታሰብ ያስጠነቀቁ ሲሆን፣ ሕዝቡ በአንድነት ቆሞ የአሜሪካና የእስራኤልን ጥቃት እንዲመክት ጥሪ አቅርበዋል።
ኢራናውያን ብርቱ አቋም በመያዝ የአያቶላህ አሊ ኻሚኒን ሥርዓት ለማስቀጠል እየሰሩ መሆናቸውም እየተነገረ ነው። ይህ የኔታንያሁ ንግግር በቀጣናው ያለውን ውጥረት ይበልጥ እንደሚያባብሰው የፖለቲካ ተንታኞች እየገለጹ ይገኛሉ።
ሁኔታዎችን አመቻችተናል በሚል የቀረበው ይህ ጥሪ፣ እስራኤል ጦርነቱን የመግታት ፍላጎት እንደሌላትና በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ በኢራን ውስጥ ሥር ነቀል የፖለቲካ ለውጥ እንዲመጣ እየገፋች መሆኑን ማሳያ ተደርጎ ተወስዷል።
