ከተለያዩ የኢትዮጽያ ክፍሎች የመጡ ከ3 ሺሕ 200 በላይ አዳዲስ ባለሙያዎች በአዲስ አበባ ከተማ መስራት የሚያስችላቸውን የሙያ ፈቃድ ማውጣታቸውን፤ የከተማ አስተዳደሩ የምግብ እና መድኃኒት ቁጥጥር ባለስልጣን ለአሐዱ አስታውቋል።
የአዳዲስ ባለሙያዎች ቁጥር ከሌሎች ዓመታት በተለየ መልኩ የጨመረው የጸጥታ ችግር ባለባቸው አካባቢዎች የነበሩ የሕክምና ባለሙያዎች አዲስ አበባ ከተማ የመስራት ፍላጎት በማሳደራቸው ነው።
የምግብ እና መድኃኒት ቁጥጥር ባለስልጣን የጤና ባለሙያዎችና ፍቃድ አሰጣጥ ቡድን መሪ ጉኡሽ አረፊ ለአሐዱ እንደተናገሩት፤ በያዝነው በጀት ዓመቱ ከ5 ሺሕ 800 በላይ ባለሙያዎች የሙያ ፈቃዳቸውን አድሰዋል።
“ከእነዚህም መካከል ከ3 ሺሕ 200 የሚበልጡት በተለያዩ የኢትጵያ ክፍሎች በመስራት ላይ የነበሩና አዲስ አበባ ከተማ ላይ ለመስራት የሙያ ፈቃድ የሚያድሱ ናቸው” ብለዋል።
“እንደ ቡድን መሪው ገለጻ ፈቃዳቸውን በአዲስ አበባ ከተማ ለመስራት የሚያድሱ የሕክምና ባለሙያዎች ቁጥር መጨመሩ በመዲናዋ የሚስተዋለውን የባለሙያ እጥረት ለማቃለል በጎ አስተዋጽኦ ቢኖረውም፤ እንደ ሀገር ሲታሰብ ግን ቀላል የማይባል ጉዳት ስለሚኖረው ሊታሰብበት ይገባል” ሲሉ አጽንኦት ሰጥተውበታል።
(አሐዱ ሬዲዮ)
