ድርጅቱ የአዕምሮ እድገት ውስንነትና ሌሎች የአካል ጉዳት ያለባቸው ህፃናትና ወጣቶች በመንፈሳዊ፣ ትምህርታዊና ሙያዊ ፕሮግራሞች በመደገፍ እንዲማሩ፤ እንዲሰሩ እንዲኖሩ የሚደግፍ መንግስታዊ ያልሆነ ተቋም ነው፡፡
ድርጅቱ ከ2014ዓ.ም ጀምሮ የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያለባቸውን ወጣቶች በ7 የተለያዩ ትምህርት ቤቶች እና በተቋሙ ግቢ ውስጥ በተለያዩ ዘርፎች ማሰልጠኑን እና ከ1ሺህ 3መቶ በላይ ለሆኑ ዜጎች ድጋፍ ማድረጉን የተቋሙ መስራች ዶ/ር ፅጌ ጥበቡ ተናግረዋል።
የራዕይ የህፃናት መርጃ ድርጅት አምባሳደር ሆና የተመረጠችው አትሌት መሠረት ደፋር፤ ሁሌም በጎ ነገሮች ላይ የመሳተፍ ፍላጎት እንደነበራት ገልጻለች፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ አይችሉም ተብለው በየቤቱ የተደበቁ ህፃናትን ወደ አደባባይ በማውጣት እና በማብቃት ለሀገር ጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ ያስፈልጋል ብላለች አምባሳደሯ፡፡
ተቋሙ ያሉበትን የቦታ፣የቁሳቁስ እጥረት ለመፍታት እና በጉምሩክ ተይዘዉ የቆዩ ኮምፒውተሮችን ለማስለቀቅ እንዲሁም ማዕከሉን ሁሉን ያሟላ ተቋም ለማድረግ እንደምትሰራ ቃል ገብታለች።
በራዕይ የህፃናት መርጃ ድርጅት እና በአትሌት መሠረት ደፋር መሀከል ለተደረሰው ስምምነት የፊርማ ስርአት በአሜሪካ እንደተከናወነ ታውቋል።
