ትራምፕ በሊባኖስ እና በእሰራኤል መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም በሦስት ሳምንት መራዘሙን አስታወቁ
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የእስራኤል እና ሊባኖስ የተኩስ አቁም በሦስት ሳምንት መራዘሙን አስታወቁ።
በሁለቱ አገራት መካከል በተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት ውይይት ላይ ምክትል ፕሬዚዳንቱ ጄዲ ቫንስ እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዩ መገኘታቸው ታውቋል።
ውይይቱ “በጥሩ ሁኔታ” ተካሄዷል ያሉት ፕሬዚዳንቱ “ዩናይትድ ስቴትስ ሊባኖስ ራሷን ከሄዝቦላህ መከላከል እንድትችል በጋራ ትሠራለች” ብለዋል።
የዚህ “ታሪካዊ ውይይት” ተሳታፊ መሆን “ትልቅ ክብር” እንደሆነ የተናገሩት ፕሬዚዳንቱ ወደፊት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ እና የሊባኖሱን ፕሬዝዳንት ጆሴፍ አውንን ለመቀበል በጉጉት እንደሚጠባበቁ ተናግረዋል።
ትራምፕ፣ የሊባኖሱ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ አውን እና የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በመጪዎቹ ሳምንታት ወደ ዋይት ሐውስ እንደሚመጡ ተናግረው አገራቸው ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ ማደራደር እንደምትፈልግ ገልጸዋል።
“ስለ ሄዝቦላህ ማሰብ አለባቸው” ያሉት ትራምፕ፣ “በዚያች አገር ነገሮችን ለማስተካከል ከሊባኖስ ጋር እንሰራለን” ሲሉ ቃል ገብተዋል።
አክለውም “ኢራን ውስጥ ከምንሰራው ጋር በአንድ ላይ እንዲሆን ማድረግ አስደናቂ ነገር ይመስለኛል” ብለዋል።

የሁለቱም አገራት ከፍተኛ ተደራዳሪዎቸ የተኩስ አቁሙ በመራዘሙ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል።
በአሜሪካ የሊባኖስ አምባሳደር ናዳ ሃማዴህ ሞዋድ፣ በአሜሪካ የእስራኤል አምባሳደር ዬቺኤል ሊተር፣ በሊባኖስ የአሜሪካ አምባሳደር ሚሼል ኢሳ እና በእስራኤል የአሜሪካ አምባሳደር ማይክ ሃካቢ እያንዳንዳቸው ትራምፕን በድርድሩ ውስጥ ላበረከቱት ሚና አወድሰዋል።
“ክቡር ፕረዚዳንት፡ በእርስዎ መሪነት ኢራን በጣም ተዳክማለች፤ ሄዝቦላህን የማዳከም እና ሊባኖስን ከወረራ ነፃ የማውጣት ዕድሉ እውን ነው” ያሉት ሌይተር፣ እስራኤል እና ሊባኖስ“ሄዝቦላህ ከተባለ ክፉ ተጽእኖ” ለማፅዳት ዓላማቸው አስተሳስረዋል ብለዋል።
ሃክካቢ ሄዝቦላህን በሰፈር ውስጥ በሁሉም ሰው መስኮት ላይ ድንጋይ ከሚወረውር ልጅ ጋር በማመሳሰል ገልጸውታል።
ሕፃኑን ማስቆም ከተቻለ በኋላ፣ እንደ ሊባኖስና እስራኤል ያሉ ሌሎች ጎረቤቶች በሰላም ይኖራሉ ሲሉም ያላቸውን ተስፋ ተናግረዋል።
