በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በገቡት ውል መሰረት ሳይለሙ ከተገኙ 158 የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች መካከል ለ114ቱ የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ የተሰጠ ሲሆን፤ 44ቱ ደግሞ ውላቸው እንዲቋረጥና ፈቃዳቸው እንዲሰረዝ መደረጉን የክልሉ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ አስታውቋል።
በሌላ በኩል ቢሮው 13 ነጥብ 361 ቢሊየን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ 66 የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች መሬት እንዲተላለፍ መወሰኑንና ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ7 ነጥብ 18 ቢሊየን ብር ብልጫ እንዳለው የቢሮው ኃላፊ ዶ/ር አባስ መሐመድ ገልጸዋል።
በተጨማሪም 187 ባለሀብቶች በግብርና፣ ኢንዱስትሪና አገልግሎት ዘርፎች ለመሰማራት ፈቃድ የወሰዱ ሲሆን ሙሉ በሙሉ ወደ ስራ ሲገቡ ከ25 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ይፈጥራሉ ተብሏል።
በተለያዩ ምክንያቶች ስራቸውን አቁመው የነበሩ 12 ኢንዱስትሪዎችም በተደረገላቸው ድጋፍ ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉ ተሰምቷል።
