በሞያሌ Mpox ቫይረስ የተያዘ ሰው መገኘቱን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር  አስታወቀ

Date:

የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢኒስቲትዩት በኦሮሚያ ክልል ሞያሌ ከተማ እስተዳደር ከሚገኙ በህመሙ መያዛቸው ከተጠረጠሩ ታማሚዎች በወሰደው ናሙና በMpox ቫይረስ የተያዘ ሰው ማግኘቱን አረጋግጧል።

ቫይረሱ እንደተገኘበት የተረጋገጠው የ21 ቀን እድሜ ያለው ህፃን ልጅ ሲሆን እናቱም በተደረገው ቀጣይ ምርመራ ለቫይረሱ እንደተጋለጠች ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡ የህፃኑ አባትም ወደ ጎረቤት ሀገር ሄዶ የነበረ መሆኑ መታወቁና የሄደባቸውን አካባቢዎች እንዲሁም ከግለሰቡ ጋር የቅርብ ንክኪ የነበራቸው ግለሰቦችን የመለየትና ክትትል የማድረግ ስራ ተጀምሯል።

ታማሚው ህፃን እና እናቱ፣ አስቀድሞ በተዘጋጀው የለይቶ ማከሚያ፣ ተገቢው የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው ሲሆን፣ እስካሁን ባለው ሁኔታ የከፋ የጤና እክል አልገጠማቸውም፡፡

የጤና ሚኒስቴር፣ በሽታው በአህጉራችን ከተከሰተበት ወቅት ጀምሮ ወደ አገር ውስጥ እንዳይገባና ከገባም ጉዳቱን ሳይከፋ በቁጥጥር ውስጥ ለማድረግ እንዲቻል በርካታ ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱ የሚታወቅ ሲሆን ለዚሁ በሽታ መካላከል ሲባል በኢትዮጵያ የህብረተሰብ ጤና ኢኒስቲትዩት ውስጥ የድንገተኛ አደጋዎች ማስተባበርያ ማዕከል ተቋቁሞ እየሰራ ይገኛል። ከዚህም ባሻገር በዚህ ቫይረስ ለመያዛቸው የተጠረጠሩ ግለሰቦች ማቆያ የሚሆኑ የተለዩ የጤና ተቋማት የተዘጋጁ ሲሆን በዚህ በሽታ የታመሙ ሰዎችን ለማከምና ተገቢውን አገልግሎት ለመስጠት የተለያዩ የጤና ተቋማት አስፈላጊውን ዝግጅት አጠናቅቀዋል።

የMpox በሽታ በተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት እየተከሰተ ያለ ህመም ሲሆን ዋና መስሪያ ቤቱን በአዲስ አበባ ያደረገው የአፍሪካ የበሽታ መከላከልና መቆጣጠር ማዕከል እና የዓለም አቀፍ የጤና ድርጅት በመተባበር በሽታውን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የተለያዩ መጠነ ሰፊ ስራዎችን በጋራ እየሰሩ ይገኛሉ፡፡ የጤና ሚኒስቴርም ከነዚህና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በሽታውን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር እያከናወናቸው የነበሩና ያሉ ስራዎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ለመግለፅ እንወዳለን።

የMpox በሽታ ቫይረሱ ካለባቸው ግለሰቦች ጋር ንክኪ ያለው ሰው የሚከተሉት ምልክቶች በሚታዩበት ወቅት ማለትም ሽፍታ፡ ሳል፣ ትኩሳት፣ ፣ የራስ ምታት፣ ድካም እና የጀርባ ህመም ሲያስተውል በአፋጣኝ ወደ ጤና ተቋማት በመሄድ ተገቢውን የምርመራና ህክምና አገልግሎት እንዲያገኝ አንዲሁም የግል እና የእጅ ንፅህና በመጠበቅና ከላይየተገለፁት ምልክቶች ባሉባቸው ታማሚዎች አካባቢ የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛዎችን በመጠቀም ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ ጥሪ እናቀርባለን። በአሁኑ ወቅት ይህ በሽታ በተወሰነ ቦታ ብቻ የታየ በመሆኑ ህብረተሰባችን ሳይደናገጥ የተለመደውን አኗኗር መቀጠል የሚችል ሲሆን ከጤና ሚኒስቴር እና ከኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የሚወጣውን ወቅታዊ መረጃዎች በአግባቡ በመከታተል ራሱን እና ቤተሰቡን ከዚህ በሽታ እንዲጠብቅ እናሳስባለን።

ጤና ሚኒስቴር

ያጋሩ!

መጽሔቶች

በብዛት የተነበቡ

ተጨማሪ ጽሑፎች
ተመሳሳይ

ከሌ/ጄነራል ታደሰ ወረደ የተላለፈ ጥሪ

በክልላችን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እያደገ የመጣው የተሳሳተ ስሌት የወለደው...

በሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ ላይ በከባድ መሳሪያዎች የታገዘ  የተኩስ ልውውጥ ተካሄደ

ለዓለም የንግድ ሰንሰለት እጅግ ስትራቴጂካዊ በሆነው የሆርሙዝ ባህረ ወሽመጥ...

የሲ.ኤን.ኤን መስራች ቴድ ተርነር ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ

የዓለማችን ግዙፍ የዜና አውታር ሲኤንኤን መስራች ቴድ ተርነር በ87...

የኢትዮጵያ አጠቃላይ ብድር 51.8 ቢሊዮን ዶላር መድረሱ ይፋ ሆኗል

ኢትዮጵያ  በድጋፍ መልክ ከአሜሪካ በየዓመቱ  በመንግስት በኩል ፈሰስ የሚደረግ...