በአዲስ አበባ ከተማ የማንበብና መጻፍ ቀን በአብርሆት ቤተ መፃህፍት እየተከበረ ይገኛል።
በመርሃ ግብሩ ላይ ንግግር ያደረጉት አምባሳደር ፍፁም አረጋ በተለያዩ ሀገራት የሚገኙ የዲያስፖራው ማህበረሰብ አባላት መፃሕፍትን አሰባስበው እና የሎጂስቲክስ ወጭውን ችለው ለቤተመጽሀፍቱ መላካቸውን ገልጸዋል።
አምባሳደሩ የዲያስፖራው ማህበረሰብ አባላት በሀገር ውስጥ ዕውቀት እንዲሰፋ የመፅሐፍት ድጋፍ ማድረጋቸው ትልቅ አስተዋፅዖ እንደሚኖረው ገልጸው መጽሀፍ ላበረከቱ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።
የአብርሆት ቤተ መፃሕፍት ዳይሬክተር ሙሉቀን ታሪኩ ቤተመፃህፍቱ በተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ድጋፍ አሁን ካለበት ደረጃ ላይ ደርሷል ብለዋል።
ዳይሬክተሩ ከአሜሪካ፣ እንግሊዝ፣ ሳውዲ አረቢያና ኬንያ ከዲያስፖራው ማህበረሰብ የተለያየ ዘርፍ ላይ ያተኮሩ መፅሐፍት ለቤተ መፅሃፍቱ መቅረባቸውን አስታውቀዋል።
ቤተመፃህፍቱ ለተለያዩ የሀገር ውስጥ ቤተ መፃህፍት ድጋፍ እያደረገ መሆኑንም አስታውቀዋል።
በመርሃ ግብሩ ላይ የዲያስፖራው ማህበረሰብ አባላት በሀገራችን ዕውቀት እንዲሰፋ የሚያደርጉትን የመፅሐፍ ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ተጠይቋል።
