የመጥፋት አደጋ ያጋጠመው ብርቅዬው ዋልያ አይቤክስ ቁጥር ወደ 306 መውረዱንና የህልውና አደጋውን ለመቀነስ ዋልያ የሚገድሉ አካላት በሐይማኖት አባቶች እንዲወገዙ መደረጉን የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ።
የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ኩመራ ዋቅጅራ ቀደም ባሉት ጊዜያት ዋልያ እንደማይታደን እና ስጋው እንዳይበላ በሐይማኖትም ተወግዞ የቆየ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህ ተግባር ከተወሰነ ዓመት ወዲህ እየተሸረሸረ መጥቶ ድምጽ አልባ በሆነ መንገድ እየታደነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
በዚህም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ብቻ የሚገኘው ዋልያ አይቤክስ በከፍተኛ መጠን የመጥፋት አደጋ እንዳጋጠመው እና በቁጥርም ወደ 306 መውረዱን አስታውቀዋል።
የዋልያ አይቤክስ ቁጥር እንዲያገግም በጋራ መስራት እንደሚያስፈልግ ለኢፕድ የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፤ በዚህም ብሔራዊ የጥበቃ ስትራቴጂ አዘጋጅቶ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ከአንድ ወር በፊት ወደስራ መግባቱን ገልጸዋል።
የ #ኢትዮጵያ ብቻ መገለጫ የሆነ ብርቅዬ ሀብት ከምድራችን እንዳይጠፋ ለማድረግና ህልውናውን ለመታደግ እንዲሁም ለመጠበቅ ከ #ደባርቅ_ዩኒቨርሲቲ ጋር በቅንጅት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
ህገ ወጥ እንቅስቃሴን ለመቆጣጠር እና የብርቅዬ እንስሳቱን ቁጥር ተመልሶ እንዲያገግም ለማድረግ “የዋልያ አምባሳደር” የተሰኘ ስያሜ የተሰጣቸው የአካባቢው ማህበረሰብ አካላትን በማደራጀት የ24 ሰዓታት የቁጥጥር ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በተጨማሪም የስሜን ተራራዎች ብሔራዊ ፓርክ አቅምን ለማሳደግ የተሽከርካሪ፣ የፋይናስ፣ የስልጠና ድጋፍ እንዲሁም የሬንጀሮችን ብዛት የመጨመር ስራ መሰራቱን ተናግረዋል።
ዋልያ አይቤክስ በኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ የሚገኝ ብርቅዬ የዱር እንስሳት መሆኑ የተረጋገጠው በ1953 ዓ.ም ሲሆን፤ በ #ዩኔስኮ የዓለም ቅርስነትም ተመዝግቧል።
Addis standard
