ሕንድ እና ፓኪስታን ከአራት ቀናት የርስ በርስ የአየር ጥቃት በኋላ “የተሟላ እና ወዲያው ተፈጻሚ የሚሆን” የተኩስ አቁም ለማድረግ መስማማታቸውን የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ አስታወቁ ። ሁለቱ ሃገራት የተኩስ አቁሙን በፍጥነት ተግባራዊ ለማድረግ መስማማታቸውን የፓኪስታን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አረጋግጧል።
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ትሩዝ በተሰኘው የራሳቸው የማህበራዊ መገናኛ መድረክ ባጋሩት መረጃ “ሌሊቱን ሙሉ ከወሰደ እና ረዥም ንግግር በኋላ ሁለቱ ሃገራት በፍጥነት ተግባራዊ የሚሆን የተኩስ አቁም ለማድረግ ” መስማማታቸውን ይፋ አድርገዋል። ትራምፕ በመልዕክታቸው ሁለቱንም ሃገራት
” ለአርቆ አስተዋይነታችሁ እና ለጋራ መረዳት ” ምስጋና ይገባችኋልም ፤ ብለዋቸዋል።
የሁለቱ ሃገራት የተኩስ አቁም ስምምነት የተሰማው ፓኪስታን በኒኩልየር የጦር መሳሪዎቿ ላይ ወሳኝ ነው የተባለው የሲቪል እና ው,ታደራዊ ባለስልጣናት ሊሰበሰቡ ነው የሚለው መረጃ ከወጣ በኋላ ነው ፤ ምንም እንኳ የፓኪስታን የመከላከያ ሚኒስቴር ጥምር ባለስልጣናቱ ለመገናኘት የያዙት ቀጠሮ የለም ብሎ ቢያስተባብልም።
ህንድ በግዛቷ በሚገኘው የካሽሜር ግዛት በውጭ የሀገር ጎብኚዎች ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መፈጸሙን ተከትሎ በፓኪስታን ግዛት ውስጥ ዘልቃ በመግባት “ሽብርተኞችን ዒላማ ያደረገ” የአየር ጥቃት ስትፈጽም ፤ ፓኪስታን በበኩሏ ለህንድ ጥቃት ተከታታይ የአጸፋ የአየር ጥቃት ፈጽማለች።
ለቀናት የቆየው እና ወደ ለየለት ጦርነት ዘልቀው እንዳይገቡ ዓለማቀፍ ስጋት አጭሮ የነበረው የኑኩልየር ባለቤት ሃገራት ግጭት ከሁለቱም ወገኖች ከስልሳ በላይ ሰላማዊ ሰዎች ሲገደሉ በርካታ ወታደራዊ እና የሲቪል መሰረተ ልማት ውድመት አስከትሏል።
