የግሉን ዘርፍ ተዋናዮችን፣ ፖሊሲ አውጪዎችንና የፋይናንስ ተቋማትን በማሳተፍ በዘላቂ ልማት፣ በማክሮ ኢኮኖሚ፣ በመዋቅራዊ እና በንግድ ዙሪያ የሚመክር የኢትዮጵያ የፋይናንስ ጉባኤ የግል ዘርፍ መድረክ እየተካሄደ ነው።
የፕላንና ልማት ሚኒስቴር፣ የገንዘብ ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በትብብር ባዘጋጁት በዚህ ጉባኤ የመንግስት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የባንክ ፕሬዝዳንቶችን ጨምሮ የተለያዩ የፋይናንስ ተቋማት መሪዎች ታድመዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ መዋቅራዊ ማሻሻያ፣ የፋይናንስ ዘርፍ ሪፎርምና የኢንቨስትመንት ዕድሎች፣ ለአካታች ፋይናንስና ልማት የብድር አገልግሎት ማመቻቸት፣ የኢንቨስትመንት ከባቢ በኢትዮጵያ እና የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ በመርሀ ግብሩ የፓናል ውይይት የሚደረግባቸው ርዕሰ ጉዳዮች ናቸው።
የኢትዮጵያ የፋይናንስ ጉባኤ የግሉ ዘርፍ መድረክ በፋይናንስ ዘርፍ ያሉ ተዋንያንን የሚያገናኝ መሆኑን የተገለጸ ሲሆን፣ ዘርፉ ለውጭ ውድድር ክፍት መደረጉን ተከትሎ በፍትሐዊነት መወዳደር የሚያስችል ስራ ለመስራት የሚያግዝ መሆኑንም ተጠቁሟል።
