በአፍሪካ ሕብረት የዲያስፖራ ጉዳዮች ክፍል ኃላፊ አንጄላ ናአ አፎሌ ኦዳይ ለአውሮፓ ሕብረት በአፍሪካ ላይ ለፈጸመው ቅኝ ግዛት እና ለአትላንቲክ የባሪያ ንግድ ካሳ እንዲከፍል ጫና ሊደረግበት እንደሚገባ ተናገሩ።
ኃላፊው ለእንግሊዝ ሚዲያ በሰጡት መግለጫ በአውሮፓና በሌሎችም ቦታዎች የቀኝ ዘመም እንቅስቃሴ እየጨመረ ቢመጣም አፍሪካ ካሳ መጠየቅ አለባት ብለዋል። “የተለያዩ አመቺ ያልሆኑ ጉዳዮች ቢኖሩም የካሳ ክፍያን ለማንሳት ከዚህ የተሻለ ጊዜ የለም” ሲሉ ተደምጠዋል ።
በየካቲት ወር የተካሄደው 38ኛው የአፍሪካ ሕብረት ጉባኤም የማካካሻ ፍትሕ እና በአህጉሪቱ ላይ ለተፈፀመው ዘር ተኮር አድልዎ መፍትሔ መፈለግ ላይ ያተኮረ ነበር።
ሕብረቱ ይህን ግብ ለማሳካት ዲፕሎማሲያዊ ጫና ከመፍጠር ባለፈ በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤቶች ሕጋዊ እርምጃ መውሰድን እንደ አንድ ስትራቴጂ እንደሚመለከት ቀደም ሲል አስታውቋል።
በዚህ ረገድ ኃላፊው የአፍሪካ ሕብረት ከአውሮፓ ሕብረት እንዲሁም ከካሪቢያን አገራት ጋር የሚያደርገው ትብብር ካሳን በተመለከተ የተቀናጀ አቋም ለመፍጠር ጠቃሚ መንገድ እንደሆነ ጠቁመዋል።
