የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የምግብና መድኃኒት ባለስልጣን የህብረተሰቡን ጤና ለማስጠበቅ እና ህገ ወጥነትን ለመከላከል በሚያደርገው የቁጥጥር ስራ ህገወጥ፣ ምንጩ ያልታወቀና ጥራት የጎደለው ሔራል የገበታ ጨዉ የተሰኘ ምርት ማግኘቱን አስታውቋል።
በዚህ ቁጥጥር ወቅት የተገኝው ሔራል የገበታ ጨዉ ምርቱ በላብራቶሪ ምርመራ ተደርጎ የአይዲድን ይዘቱ ከደረጃ በታች የሆነ ፣የምርት መያዣ ከረጢቱ ደረጃዉን ያልጠበቀ እና ታሽጎ ለገበያ የቀረበዉ ምርት የንፅህና ጉድለት እና ባዕድ ነገር ያለበት መሆኑ ተደርሶበታል።
በተጨማሪም ድርጅቱ ሔራል የገበታ ጨዉ በሚል ስያሜ ከአዲስ አበባ ምግብ እና መድኃኒት ባለስልጣን የጤና ብቃት ማረጋገጫ ሳያወጣ የብቃት ማረጋገጫ እንዳወጣ በማስመሰል እና የጨዉ መያዣ ከረጢቱ ላይ ባልተገባ መልኩ የባለስልጣን መስሪያ ቤቱን ስም በመጥቀስ ተጠቃሚዉን ማህበረሰብ በማጭበርበር በገበያ ላይ ምርቱ የተሰራጨ መሆኑ ተደርሶበታል።
የባለስልጣኑ የምግብና ጤና ነክ ቁጥጥር ዳይሬክቶሬት አቶ እስጢፋኖስ ጌታቸው ለብስራት ሬዲዮ እንደገለፁት ባለስልጣኑ በገበያ ላይ የተሰራጨው የጨው ምርት የጤና ጉዳት ሊያስከትል ስለሚችል ህብረተሰቡ እንዳይጠቀመው በመግለፅ ምርቱን የሚመለከተው አካል እንዲሰበስበው መደረጉን ተናግረዋል።
በተጨማሪም ባለስልጣኑ በተሰጠው ስልጣን እና ኃላፊነት መሰረት ድርጅቱ የብቃት ማረጋገጫ ሳያወጣ በህገወጥ መንገድ ምርቱ በገበያ ላይ በማዋል ፣ ከደረጃ በታች የሆነ ምርት ለህብረተሰቡ በማቅረብ ፣የባለስልጣን መስሪያ ቤቱን ስም በህገወጥ ምርት ህጋዊ አስመስሎ በመጠቀም እና የንፅህና ጉድለት እና ባዕድ ነገር ያለበት ምርት ለገበያ በማቅረቡ አምራች ድርጅቱ በህግ እንዲጠየቅ አድርጓል፡፡
ህብረተሰቡ በዚህ ጉዳይም ሆነ መሰል ህገ ወጥ ተግባራትን ሲመለከት በ8864 ነጻ የስልክ መስመር ጥቆማ ሊሰጥ ይገባል ሲሉ አቶ እስጢፋኖስ ጌታቸው ጨምረው ተናግረዋል።
ለብስራት ሬዲዮ
