ሕዳር 21ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ) ቻይና የዓለምን የሳይበር ደህንነት እና ዓለም አቀፍ መረጋጋትን ስጋት ላይ የሚጥል ኃይለኛ የባህር ውስጥ የኬብል መቁረጫ መሳሪያ ይፋ ማድረጓ ተሰምቷል።
ከዓለማችን የኢንተርኔት ትራፊክ ውስጥ 95 በመቶውን የሚሸከሙትን በአረብ ብረት የታጠቁ የባህር ውስጥ ኬብሎችን መበጣጠስ የሚችል ይህ መሳሪያ በቻይና የመርከብ ሳይንስ ምርምር ማዕከል የተሰራ መሆኑ ታውቋል።
ይህ አዲስ መሳሪያ እስከ 4,000 ሜትር ጥልቀት ባለው የባህር ውስጥ መስራት የሚችል ሲሆን፣ ኬብሎቹን ለመቁረጥ ደግሞ አልማዝ የተሸፈነ መቁረጫ ይጠቀማል።
በይፋ ለባህር ላይ አደጋ ግልጋሎት እና ለሀብት ማውጣት ታስቦ ቀርቧል ቢባልም፣ እንደ ጉዋም ባሉ ስትራቴጂካዊ ቦታዎች አቅራቢያ ሊኖረው የሚችለው ወታደራዊ አጠቃቀም በመከላከያ ባለሙያዎች ዘንድ ከፍተኛ ስጋት ፈጥሯል።
በተጨማሪም መሳሪያው በባህር ውስጥ በሚሰሩ ሰርጓጅ መርከቦች አማካኝነት በድብቅ ወደ ቦታው ሊላክ መቻሉ፣ እንደ ቴክኖሎጂ ትልቅ ስኬት ቢቆጠርም፣ እንደ ስትራቴጂካዊ ስጋትም ይታያል።
የቻይና ሳይንቲስቶች ለሰላማዊ ዓላማ ነው ቢሉም፣ የዓለም የኢንተርኔት መሠረተ ልማት በአብዛኛው በባህር ውስጥ ኬብሎች ላይ የተመሰረተ በመሆኑ፣ የዚህ መሳሪያ ባለ ሁለትዮሽ ዓላማ የባህር ውስጥ የመሰረተ ልማት ጥቃት ፍራቻን አባብሶታል።
በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው የጂኦፖለቲካ ውጥረት እየጨመረ በመጣበት በዚህ ወቅት፣ ይህ የቴክኖሎጂ እድገት ዓለም አቀፍ የኃይል ሚዛንን የመቀየር እና እርስ በርስ የተያያዘው ዓለማችን ያለበትን አደገኛ ተጋላጭነት የሚያሳይ ነው።
