በአዲስ አበባ ከተማ የህብረተሰቡን ጤና ለመጠበቅ በተከናወነ መጠነ ሰፊ የቁጥጥር ዘመቻ፣ ደንብ በተላለፉ 875 የምግብና ጤና ተቋማት ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን የአዲስ አበባ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን አስታወቀ።
ባለፉት ሰባት ወራት በማዕከልና በ11ዱም ቅርንጫፎች በተካሄደው በዚህ ኦፕሬሽን፣ 733 ተቋማት የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸው ሲሆን፣ 119 ተቋማት ደግሞ በጊዜያዊነት እንዲታሸጉ ተደርጓል።
ከዚህም ባለፈ ከፈቃድ ውጭ ሲሰሩ የተገኙ 3 ተቋማት ፈቃዳቸው እንዲሰረዝ ሲወሰን፣ 20 ተቋማት ደግሞ የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባቸዋል።
በቁጥጥሩ ወቅት ጥራት የሌላቸውና ለጤና አስጊ የሆኑ፣ ግምታዊ ዋጋቸው ከ52.6 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጡ የምግብና ጤና ነክ ምርቶች እንዲሁም የትምባሆ ህግን ተላልፈው የተገኙ
ውጤቶች እንዲወገዱ ተደርጓል።
የባለስልጣኑ የምግብና ጤና ነክ ተቋማት ቁጥጥር ዳይሬክተር አቶ እስጢፋኖስ ጌታቸው እንደገለጹት፤ ተቋማት የተቀመጠውን ስታንዳርድ ጠብቀው እንዲሰሩ የክትትልና የድጋፍ ስራው ተጠናክሮ ይቀጥላል።
ይህ እርምጃ በከተማዋ ያለውን የምግብና የመድኃኒት ደህንነት አስተማማኝ ለማድረግ የተከናወነ የቁጥጥር ስራ አካል መሆኑ ተመላክቷል።
