የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከደቡብ ኮሪያ ሪፐብሊክ መንግሥት ጋር በመተባበር የኤሌክትሪክ ታሪፍ ድርድር ማዕቀፍን ለማዘመን የሚያስችል የጥናት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ማካሄዱን አስታወቀ።
ይህ ጥናት ተቋሙ ያለበትን የፋይናንስ ውስንነት በመቅረፍና አሰራሩን ከዓለም አቀፍ ስታንዳርዶች ጋር በማስማማት ረገድ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ተብሏል።
የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አሸብር ባልቻ እንደገለጹት፤
ኢትዮጵያ ሰፊ የታዳሽ ኃይል ሀብት ቢኖራትም፣ የኃይል ተደራሽነትን ለማስፋፋት የፋይናንስ አቅምን ማጠናከር ወሳኝ ነው። ለዚህም ደግሞ በሥራ ላይ ያሉ የታሪፍ አሰራሮችንና የድርድር ማዕቀፎችን ማዘመን ቀዳሚው ተግባር መሆኑን ገልጸዋል።
ይህ የኤሌክትሪክ ታሪፍ ድርድር ማዕቀፍን የማዘመን ፕሮጀክት፤ በደቡብ ኮሪያ መንግሥት በሚደገፈው የዕውቀት ሽግግር ፕሮግራም ሥር በዓለም አቀፍ ደረጃ ከቀረቡ ከ400 በላይ ፕሮጀክቶች መካከል አሸናፊ በመሆን የተመረጠ መሆኑን የኢትዮ-ፓወር አካዳሚ ዳይሬክተር ወንድወሰን ካሳ ገልጸዋል።
ጥናቱ በደቡብ ኮሪያ ባለሙያዎች ድጋፍ የሚከናወን ሲሆን፣ የተቋሙን ባለሙያዎች አቅም በመገንባትና የአሰራር ዘመናዊነትን በማምጣት ረገድ የላቀ ሚና እንደሚኖረውም ተመላክቷል።
በጥናቱ ማጠቃለያ ላይ የሚቀረጸው አዲሱ የታሪፍ ድርድር ማዕቀፍ፤ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይልን የፋይናንስ ቁመና በማጎልበት፣ የግል ኢንቨስትመንቶችን በማበረታታትና የኢንቨስትመንት ስጋቶችን በመቀነስ ተቋሙ ተልዕኮውን እንዲያሳካ ከፍተኛ አስተዋፅዖ እንደሚኖረው ታምኖበታል።
