የጅቡቲ ወደቦች እና ነፃ የንግድ ቀጠናዎች ባለሥልጣን በባሕረ ሰላጤው ቀውስ ሳቢያ ወደኋላ ተመልሰው የሚታሰቡ (retroactive) ተጨማሪ ክፍያዎችን ማገዱን አስታወቀ።
የባለሥልጣኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቡበከር ዑመር ሃዲ እንደገለጹት፤ ውሳኔው በዕቃና በመርከብ ባለቤቶች መካከል ፍትሃዊነትን ለማስፈን የታለመ ነው። ይሁን እንጂ ‘ግሬኮ’ የተሰኘው የኢንሹራንስ ብሮከር የዓለም አቀፍ መርከብ ትራንስፖርት በከፍተኛ ጫና ውስጥ መሆኑን ጠቁሟል።
ይህም ከውጭ ንግዷ 95 በመቶ በላይ በጅቡቲ ላይ ለምትተማመነው ኢትዮጵያ ብርቱ ስጋት ሆኗል። በ2017 ዓ.ም ብቻ 9.5 ሚሊዮን ቶን ዕቃ በወደቡ ያስለፈችው ኢትዮጵያ፣ ለወደብ አገልግሎት እስከ 2 ቢሊዮን ዶላር እንደምትከፍል ይገመታል።
ይህ ወጪ ሀገሪቱ ከውጭ ንግድ ከምትጠብቀው አጠቃላይ ገቢ ውስጥ ሲሰላ የአንድ ሦስተኛ ገደማ ድርሻ ያለው በመሆኑ፣ የወደብ ክፍያዎች መናር በኢኮኖሚዋ ላይ የሚፈጥረው ጫና ቀላል እንደማይሆን ተመላክቷል።
