በአዲስ አበባ ከተማ የሚንቀሳቀሱ ተሽከርካሪዎች የሚለቁት በካይ ጋዝ ለነዋሪዎች ጤና፣ በተለይም ለሕፃናትና ለአረጋውያን ከፍተኛ ስጋት እየደቀነ መሆኑን የከተማዋ ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ።
ቢሮው በቅርቡ ባደረገው ድንገተኛ የልኬት ምርመራ ከተመረመሩ 75 ተሽከርካሪዎች መካከል ሲሶ የሚሆኑት ከተፈቀደው መጠን በላይ ጋዝ እንደሚለቁ አረጋግጧል።
ይህ የብክለት ችግር በግል ተሽከርካሪዎች ላይ ብቻ ሳይወሰን በመንግሥት ተቋማት መኪኖች ላይም የታየ ሲሆን፣ ችግሩን በዘላቂነት ለመቅረፍ “የተሽከርካሪ በካይ ጋዝ ልቀት ቁጥጥር መመሪያ ቁጥር 1051/2017” ተፈጻሚ መደረግ ጀምሯል።
በተጨማሪም የትራንስፖርት ቢሮው የተሽከርካሪ ምርመራ ተቋማት (ቦሎ ሰጪዎች) ከሙስና በጠራ መልኩ ሙያዊ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ጥብቅ ማሳሰቢያ አስተላልፏል።
በአሁኑ ወቅት የከተማ አስተዳደሩ በስሩ የሚገኙ ተሽከርካሪዎች የጋዝ ልቀትን የሚቀንሱ ቴክኖሎጂዎችን እንዲገጥሙ ግዴታ የጣለ ሲሆን፣ የግል ባለቤቶችም መሰል እርምጃዎችን እንዲወስዱ ጥሪ ቀርቧል።
ይህም የከተማዋን የአየር ጥራት ለማሻሻልና በካይ ጋዝ የሚያስከትለውን የጤና እክል ለመቀነስ የታለመ የተቀናጀ ጥረት አካል መሆኑ ተመላክቷል።
