የኡጋንዳ አየር መንገድ ተቋርጦ የነበረውን የረጅም ርቀት በረራ ለማስቀጠል እንዲረዳው ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር የ”Wet-lease” ኪራይ ስምምነት መፈራረሙ ተገልጿል።
በስምምነቱ መሰረት ET-ASI የተመዘገበ ቦይንግ 787-8 ድሪምላይነር አውሮፕላን ከ43 የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰራተኞች ጋር ኢንቴቤ ገብቷል።
ይህ አስቸኳይ ውሳኔ የተላለፈው የአየር መንገዱ ሁለት ኤርባስ አውሮፕላኖች ባልታሰበ የጥገና ምክንያት ከአገልግሎት ውጪ በመሆናቸው ነው።
አየር መንገዱ ይህንን እርምጃ የወሰደው በተለይ የለንደን ጋትዊክ በረራ እንዳይቋረጥና በአቪዬሽን ህግ መሰረት ስራ በሚበዛባቸው አውሮፕላን ማረፊያዎች የተሰጠው የበረራ ሰዓት እንዳይቀማ ለመከላከል ነው።
ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ የአየር መንገዱን ክፍተት ለመሙላት የቀድሞውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ግርማ ዋቄን በአማካሪነትና በተጠባባቂ ስራ አስፈፃሚነት መመደባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ አየር መንገዱ ለተሳፋሪዎቹ አማራጭ መፍትሄዎችን እያመቻቸ መሆኑን አስታውቋል።
